
ሰኔ 01/2018 ዓ.ም
የወልድያ ዩኒቨርሲቲ ለተማሪዎቹ፣ ለሰራተኞቹ እንዲሁም ለአካባቢው ማህበረሰብ የሚሰጠውን ሁለንተናዊ አገልግሎት ይበልጥ ለማሳደግ ታስቦ የተደራጀው የስፖርት ጂምናዚየም ማዕከል አስፈላጊ የሆኑ ቁሳቁሶችን አሟልቶ በዛሬው ዕለት በይፋ ስራ ጀምሯል።
ማዕከሉ በይፋ ስራ መጀመሩን ያበሰሩት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር አነጋግረኝ ጋሻው ባደረጉት ንግግር ዩኒቨርሲቲው በመማር ማስተማር አዕምሮው የጎለበተ ትውልድን ብቻ ሳይሆን የተሟላ ስብዕና ያለው እና ጤንነቱ የተጠበቀ፤ በአካልም የጎለበተ ትውልድን ለመፍጠር ጂምናዚየሙ ስራ መጀመሩ ያለው ሚና ከፍተኛ ነው ብለዋል።
በማዕከሉ ለስፖርቱ ቅርበት ያላቸው አካላት ብቻ ሳይሆን ሌላው የግቢውም ሆነ የአካባቢው ማህበረሰብ እንዲጠቀሙበት ማድረግ ያስፈልጋል ያሉት ፕሬዝዳንቱ፤ የስፖርት ባህል እንዲዳብር የተጀመሩትን በማስቀጠልና በማጠናከር ሁሉም በትኩረት መስራት እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።
የአስተዳደርና ቢዝነስ ልማት ም/ፕሬዝዳንት ዶ/ር በላይ መንግስቴ በበኩላቸው ስፖርት በአዕምሮ፣ በአካልም ሆነ በስነ-ልቦና የጎለበተ እንዲሆን የሚያደርግ በመሆኑ ይህንን ጂምናዚየም ሁሉም ባለድርሻ አካላት ጠብቆና ተንከባክቦ በአግባቡ ሊጠቀምበት ይገባል ሲሉ አሳስበዋል።
የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት ያስተላለፉት የተፈጥሮና ቀመር ሳይንስ ኮሌጅ ዲን ዶ/ር ደርበው ንጉሴ ማዕከሉ ደረጃቸውን የጠበቁ ዘመናዊ የስፖርት ቁሳቁሶች የተሟሉለት በመሆኑ የመማር ማስተማር ሂደቱ ከንድፈ-ሃሳብ በተጨማሪ በተግባር የተደገፈ ጥራት ያለው ትምህርትን ከመስጠት ባለፈ በሳይንስና ቴክኖሎጂ የታገዘ የተለያዩ የአካል ብቃት ስልጠናዎችን ለመስጠት ያስችላል ብለዋል።
በማዕከሉ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ፣ የደም ግፊትና የስኳር መጠንን መለካት፣ በማሽን የታገዘ ማሳጅ፣ በባለሙያ የታገዘ የማማከርና ሌሎች መሰል አገልግሎቶች እንደሚሰጡ የገለጹት የስፖርት ሳይንስ ት/ት ክፍል ኃላፊ መምህር የሸዋስ ጀምበሩ ናቸው።
መ/ር የሸዋስ አክለውም ማንኛውም የግቢውም ሆነ የአካባቢው ማህበረሰብ ወደ ማዕከሉ በመምጣት የአገልግሎቱ ተጠቃሚ እንድትሆኑ ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
በመርሃ-ግብሩ ላይ ተገኝተው ማዕከሉን የጎበኙ የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ በየደረጃው ያሉ የስራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው ተሳታፊ እንግዶች በሰጡት አስተያየት በማዕከሉ መከፈት የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል።
ዘገባው የወልድያ ዩኒቨርሲቲ የህዝብና አለም አቀፍ ግንኙነት ነው።
‹‹አእምሮ ሲከፈት፤ ዓይኖች ማየት ይችላሉ›› ‹‹ Open Mind, Open Eyes!››
የተቋሙን ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፤
Web site: https://wldu.edu.et/
Facebook : https://www.facebook.com/WoldiaUniversity
Telegram Channel: https://t.me/Woldia_University
YouTube: https://www.youtube.com/channel/UCHt88As5v2BmynWine1Oexw
P.O.Box = 400
Woldia Town, Amhara Region, Ethiopia.